Рет қаралды 263,040
እግዚአብሔርም ለሚወዱት እንደ ሃሳቡም ለተጠሩት ነገር ሁሉ ለበጎ እንዲደረግ እናውቃለን እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ በሮሜ መልእክቱ 8፤28። ሁልጊዜ እግዚአብሔርን ያለ ማቋረጥ በትእግስት ልንጠብቀው ይገባል። የጻድቁ የዮሴፍን ታሪክ ብንመለከት ወንድሞቹ በቅንአት መንፈስ ተነሳስተው በሸጡት ጊዜ ሥራቸው ክፋትና ጭካኔ የተሞላበት ነበር። ነገር ግን እግዚአብሔር አምላክ ያንን የክፋትና የተንኮል ሥራቸውን አይቶ ወደ በጎ ለወጠው። ዮሴፍንም በሰው ሃገር በፈርዖን ላይ ተሹሞ ሕዝቡም ሁሉ ለቃሉ ታዛዥ፤ በፈርዖን መንግስት ሁለተኛ ባለ ሥልጣን እንዲሆን አደረገው። ጻድቁ ዮሴፍም ለወንድሞቹ እንዲህ ብሏቸው ነበር፤ እናንተ ክፉ ነገርን አሰባችሁብኝ እግዚአብሔር ግን ብዙ ሕዝብ እንዲድን ለማድረግ ለመልካም አሰበው ዘፍ 45። ምንጊዜም ሐሰትና ክፉ ነገሮች የሚመነጩት ከዲያብሎስ ቢሆንም “አቤቱ ወደ ፈተና አታግባን” ብለን ሁልጊዜ ልንጸልይ እና እግዚአብሔርን ልንማጸን ይገባል። አንድ ሰው ቀለል ባለ በሽታ በመዳኑ ምክንያት ፈጣሪውን ካመሰገነ፤ በሕይወቱ ውስጥ ለትንንሽ ነገሮች የሚያመሰግን መሆኑን ያመላክታል። በአንጻሩም አንዳንድ ሰዎች ገና የትምህርት ውጤት እንደጠበቁት ስላልመጣላቸውም ይሁን በኑሯቸው ሁኔታ ስላልተደሰቱ ብቻ እግዚአብሔርን በትንሽ በትልቁ የሚያማርሩ፤ ባልፈጠርኩ ይሻለኛል እስከማለት የሚደርሱ ብዙ ናቸው፤ ይህ ደግሞ ተገቢ አይደለም። ቅዱሳን አባቶች “ጸጋ ያለ ምስጋና አያድግም” እንዳሉ በማንኛውም ጊዜና ወቅት እግዚአብሔርን ተመስገን ማለት ተገቢ ነው። ምስጋና የማያቋርጥ በረከት ያለው ስለሆነ ካገኘን ፈተና እንድናለን፤ የመጣብንን ፈተና በትእግስት ልንወጣ ያስፈልጋል ምሳሌውንም ከኢዮብ እንማራለን።
Kesis Zebene Lemma