Рет қаралды 99,707
Subscribe, Share, Like, Comment እያደረጋችሁ ላልሰሙት አሰሙ ላልነቁ አንቁ! መንፈሳዊነት ይብለጥ! የማዳመጥ ጊዜ ላይ ነን!!!
ዲያቢሎስ ትልቁ ሥራውና ግቡ የክስ መዝገብ ላይ ኃጢአታችንን ከጽድቅ ሥራችን አብዝቶ መደርደር ነው፡፡ ከመወለድ አንስቶ፤ የሕይወት ቆይታችን ባላንጣ ለመሆን ነፍስ አውቀን መንቀሳቀስ በጀመርንባት እያንዳንዷ ዕለት ላይ፤ በየቀኑ ኃጢአት እንድንሠራ በተለያዩ ስውርና ግልጽ መንገዶች በመፈተን፤ የጥፋት መዝገቡ ላይ የኃጢአታችንን ጽሕፈት ይከትባል፡፡
ርኩሳን መናፍስት እና ኃጢአት በአንድ ገለጻ ውስጥ የተሣሠሩ የልዑል እግዚአብሔር መልካም ነገራት ተጻራሪ ሠራተኛ እና ሥራ ናቸው፡፡ ቅዱሳን ጽድቅን ይፈጽማሉ፡፡ ርኩሳን ኃጢአትን ያደርጋሉ፡፡ አጠር ባለ ገለጻ፤ 'ኃጢአት እየሠራን በመጣንበትና እየሠራን በቀጠልንበት ልክ፤ ሕይወታችን ውስጥ ያሉት መናፍስትም ቁጥራቸውና ሥራቸው በዛው ልክ ነው፡፡" ይህም ቅልብጭ ባለ ቋንቋ፤ ኃጢአት የሚሠራ ሰው ሁሉ ውስጥ ያደፈጡ የርኩሳን መናፍስት ኃይል በኑሮው ውስጥ አለ፡፡ ምክንያቱም ኃጢአት የአጥፊ መንፈሶች ግብር ውጤት ነው፡፡
በሚያሳዝንና ግርምትም በሚፈጥር ደረጃ በዛሬ ጊዜ ያሉ የሃይማኖት አባቶችና አገልጋዮች፤ ኃጢአትን እና ክፉ መናፍስትን ለያይተው አይተው እንዲሁ ለምዕመኑ ለያይተው ያሳዩታል፡፡ እጅግ የበዙ ሰዎችም በደፈናው "ንስሐ ግቡ!" ሲሉ እንጂ፤ "በኃጢአት አረንቋ ያሰራችሁ ዲያቢሎስ ነውና እርሱን በመፋለም እየበረታችሁ ንስሐ ግቡ" ሲሉ አይደመጡም፡፡ በመሆኑም ብዙዎቻችን ሰይጣን ያለ የሚመስለን በጣም ክፉ የሆኑ ሰዎች ጋር ብቻ፣ ፍጹም አምላክን የካዱ ሰዎች ጋር ብቻ፣ ፈቅደው ወደ ሕይወታቸው ጠርተው የሚጠቀሙት ሰዎች ጋር ብቻ፣ በየቤተክርስቲያናቱ አሊያ በየገዳማቱ ጸበል ቦታ የሚጮኹት ጋር ብቻ ነው የሚል ራስን ከመናፍሰት ወጥመድ የማራቂያ መስፈርት አውጥተን፤ እኛ ከኃጢአት አሠሪዎች ስውር አገዛዝ ነጻ እንደሆንን በዘመናዊነታችንና ትንሽም ብቅ ጥልቅ በምናደርጋት ክርስትናችን ተማምነን የተቀመጠን እጅግ ብዙ ሰዎች አለን፡፡ ይሄ በጣም አስቸጋሪው ነገር ነው ወገኖቼ፡፡ ግን እዛ ጸበል ቦታ ተገልጦ ሌላ ሰው የጮኸውን ጩኸት እኛም እያንዳንዳችን በየግል በየግላችን እንጮኸዋለን፡፡ ጤና በማጣት እንጮኻለን፣ በረከት በማጣት እንጮኻለን፣ ፍቅርና ደስታ በማጣት እንጮኻለን፣ ጸጋና እውነት በማጣት እንጮኻለን፣ በቤተሰብና በትዳር ሕይወት ሰላም ማጣት እንጮኻለን፡፡
እግዚአብሔርን በአፍ አመልካለሁ ብለን በተግባር ስንከዳው፤ በአንጻሩ ሰይጣንን በአፍ ከድቻለሁ ብለን በተግባር አብረነው ስንኖር፤ "እኔ መንፈስ የለብኝም" እያልን በ'የለብኝም" ድምፅ ይበልጥ እንደሌለ ሆኖ የሚቀመጥበትን ጊዜ እያረዘምንለት፤ በኛ ባሕሪይ ውስጥ ምሽግ ሰርቶ የሚያደፍጥበትን አቅም እያሳደግንለት፤ የክፉ መንፈስ መግለጫ የሆነውን ኃጢአት ግን እንደልብ እየሠራን በእግዚአብሔር ነገራት ላይ ድንዝዝ ብለን ስንቀመጥ፤ "ምንድነው ነገሩ? ለምንድነው በእምነቴ ውስጥ በእውነተኛ ምግባር መመላለስ ያቃተኝ? እውነት ከመንፈስ የጸዳሁ ሰው ብሆን ኖሮ ኑሮዬስ ከጥፋት ገጽታዎችና የኩነኔ ተግባራት ለምን ጸድቶ አይታይም? ኃጢአትን ያለማቋረጥ እየሠራው የኃጢአት ኃይል የሆነው የዲያቢሎስ መንፈስ የለብኝም ማለት እንዴት ይስማማል?" ብለን አንመረምርም፡፡
ዓለማችን በተለይ በዚህ ዳፍንታም ዘመኗ፤ ዓለም ላይ ገዢ ሆኖ በእያንዳንዱ የሰው ልጅ ሕይወት ውስጥ የጥፋትና የማጥፋት መሪ ሆኖ የተቀመጠው ጠላት ላይ የመንቃትን እውነት ፈጽማ አውጥታ፤ ይልቁኑ ኃጢአትን ለምዳና የሕይወት አንድ ጉዳይ አድርጋ ከጊዜያት ግስጋሴ ጋር በሚጨምር የእርግማን፣ የርኩሰትና የክፋት ገጽታዎች የተሞላች ስትሆን ጊዜ ጽድቅ ኃጢአት፥ ኃጢአት ደግሞ ጽድቅ ሆኖ ተገልብጦ ቁጭ አለ፡፡
ሰዎችም ታዲያ በዘመናት መካከል ስንመላለስ፤ የቅድስና እውነታዎችን እንደ ባርነት እንድንቆጥር በሥጋ ምቾት ውስጥ የተደበቁት ኃጢአቶች የዕለት ክስተቶቻችን ሆነው እንዲላመዱን፤ በጽድቅ አምባዎች ላይ መቆም በዓለም ውስጥ የሚገባንን ኑሮ እንዳንኖር የተገዢነት ቀንበር የሚያሳርፍ ተጽዕኖ እንዳለው ክፉ መናፍስቶች በቀላልና በሚስማማን የስልት ጥበብ ሲያሳምኑን፤ የፉክክር ትልቅ መድረክ ሆና በተቀረጸቺው የርዮተ ዓለም አካሄድ ውስጥ አሸናፊ ለመሆን የርኩሰትንና የኃጢአትን ግብራት መፈጸም አስፈላጊ እንደሆነ በጋራ ስምምነት ተወስዶ፤ "ኃጢአት የማይሠራ ሰው የለም" እያልን እርግማንን በነጻ እያስተዋወቅን፣ ግፍን በነጻ እያጸደቅን፣ ርኩሰትን በነጻ እያስፋፋን፤ "ሁሉም ሰው ኃጢአት ይሠራልና እኔም በዚህ ሁሉነት ውስጥ የደርሻዬን ኃጢአት ልውሰድ" የሚል የየግል ሕይወትን እየመራን፤ የከሳሻችንን ዲያቢሎስ የኃጢአት መዝገብ እያሳደግንለት የነፍሳችንን ጩኸት አፍነን የሥጋችንን ሹክሹክታ እየሰማን ዝም ብለን ቀን እንቆጥራለን፡፡
ከኃጢአት ጋር በዘልማድ በመኖር ቆይታ ውስጥ የኃጢአት ውጤት የሆነውን መከራን ከመልመድ ዝንባሌዎች መካከል ለዘመናት ችግርን ተዳብለነውና ተስማምተነው ስናበቃ፤ በዕለት ክሰተቶች የታጠረ፥ በምኞቱ ግን የሥጋ ምቾትን አብዝቶ የናፈቀ ኑሮን የመኖሩ ቦታ ላይ የድንዛዜ አካኋን ይዘን፤ ያንኑ አኗኗሪ ችግርን ወደፊት ያለ ለውጥ እያስቀጠልን እስከአሁን የመጣን ስለሆንን፤ ዛሬ ዛሬ መፍትሔዎች ያደናግሩናል፡፡ ከችግርና ከመከራ የመላቀቂያ መንገዶች አዲስ ይሆኑብናል፡፡ ግር ይሉናል፡፡ አልፎም ተርፎ ወደ ቅድስና ሐሳቦችና የመፍትሔ መስመሮች ላይ ለመድረስ ዋጋና መሥዋዕትነት መክፈል፤ ካለንበት የጋራ ማጥ አንፃር ለየግላችን ትከሻ የከበደ መስሎ ስለሚሰማን፤ ወደሚሻለው ጎዳና ለመጓዝ የምናሳየው ፍቃድና ፍላጎት ግልጽ ያልሆነ፣ ሁሌ ጎትጓች የሚጠይቅ፣ እየመላለሰ ተነሣሽነትን የሚፈልግ እና የመፍትሔ ጉዞው ሳይጀምርም ሆነ የተወሰነ ተጀምሮ፥ በድካም አማራጮች የተከበበ በመሆን፤ ይኸውና በዚህ ስለዚህ የዘመኑ ትውልድና ጊዜው፥ እንደጋራም እንደተናጠልም ብዞ ቦታ ላይ ተቸግሮ ይገኛል፡፡
ሰዎች ሆይ፥ በእውነት በጣም አስቸጋሪ ዘመን ላይ እንገኛለን፡፡ ኃጢአትን በመልመድ የኖርንበት ዘመን የእግዚአብሔርን ፍቅር ከሰው ባሕሪይ ውስጥ አሳጥቶ አረመኔያዊ ጨካኝ የሰው ባሕሪያትን አስገኝቷል፡፡ ኃጢአትን በመልመድ የቆየንበት ኑሮ የእግዚአብሔር ጽድቅ በእጅጉ ርቆበት፤ አረማዊ ጊዜያት እንዲነግሡበት ተገድዶ ይገኛል፡፡ ኃጢአትን በመልመድ ያሳለፍነው ዕድሜ አጥፊ መናፍስቶችን አበልጽጎ ሲገኝ፤ ዛሬ ቅዱስ መሆን ተዓምር እስከሆነበት ጥግ ድረስ የጋራ እርግማን ተስማምቶን፤ ስለ ነፍስ መጨረሻ መጨነቅ አቅቶን፤ የደመወዝ ቀን መጨረሻ እያስጨነቀን፣ የሥጋ ምቾት መጀመሪያው እያስጨነቀን፣ የውስጥ ሕይወታችን ባላወቅነው ደባል ጠላት በአዚምነት ድብዛዜ መካከል ተደብቆ ይገኛል፡፡ ትልቁ ደግሞ ለዲያቢሎስ በእጅጉ ተመችቶት የመቆጣጠር ሥልጣኑን በሕይወታችን ውስጥ እንዲያሰፋ ያደረገው ጉዳይ፤ የነፍሳችን መጨረሻ እንደሚመጣ ማሰብ ያለመቻላችን ጉዳይ ነው፡፡ ከላይ የተመለከትነው ቃል እስኪ ምን ይላል? "ቀንና ሌሊትም በአምላካችን ፊት የሚከሳቸው የወንድሞቻችን ከሳሽ ተጥሎአልና።" በአምላካችን ፊት የሚለው ቃል የነፍሳችንን የመጨረሻ ሁኔታ ላይ ግንዛቤ ይሰጣል፡፡ አሁን እኮ የመጨረሻው ጊዜ ሲመጣ በአምላኩ ፊት ሊቆም ግድ እንደሆነ የሚያስታውስ ሰው ጠፋ፡፡ ቤተሰብም፣ ልጅም፣ ተማሪውም፣ አስተማሪውም፣ ነጋዴውም፣ ባለሥልጣኑም፥ ሁሉ በየዘርፉ ያለው አንድ ቀን በአምላኩ ፊት ነፍሱን ይዞ እንደሚቀርብ ፍጹም ረሳ፡፡ ቢዘገይ የቀረ መስሎን ይሆን?
ታዲያ ምን ይሻላል? እንዴት ነው ነገሩ? ከኃጢአት ጋር ግብግብ ገጥመን ልናሸንፍ አይገባምን? በየቀኑ አሸምቆ የመጥለፊያ አሽክላ እያስቀመጠ በኃጢአት ወድቀን ስንገኝ የመክሰሻ ዝርዝሩን የሚጨምብርንን ጠላት ማስቆም አያስፈልግምን? ዘመናችን አልቆ ነፍሳችን ወደጌታ ፊት በቆመች ጊዜ የምንሆነውን ማሰብ አያስጨንቀንምን? ስለዚህ ምን እናድርግ?
በራሳችን የሥጋ ፈቃድ በመናፍስት ግፊትና ኃይል በኩል ኃጢአት ከመሥራት ሙሉ በሙሉ ማቆሞ እንቸል ዘንድ አዳጋች ነው፡፡ በተለይ በዚህ ኃጢአት ጽድቅ፣ ሌብነት የሥራ ክፍል፣ ውሸትና ሐሜት የዕለት እንጀራ፣ ርኩሰት ቅድስና፣ እርግማን ምርቃት፣ ፍቅር ጥላቻ፣ ሰላም ረብሻ፣ ደስታ ሐዘን፣ ዝሙት የሥልጣኔ መግለጫ በሆነበት በዲያቢሎስ ዘመን፤ ዓለም ውስጥ በዘልማድ ከምንመላለስበት ኑሮ ወጥተን በአንድ ጊዜ ከኃጢአት ግብራት መራቅ ጊዜ ይወስዳል፡፡ ነገር ግን ጊዜ ይወስዳል እንጂ አይቻልም የሚል ነገር አልተነገረም፡፡ ቀድሞውኑ የተጠራነውንም ኃጢአትን በሙሉ ከኑሮአችን ላይ አርቀን ሁላችን ቅዱስ የሆነ ሕይወትን መኖር እንዲገባን ነው፡፡ "ዳሩ ግን። እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁኑ ተብሎ ስለ ተጻፈ የጠራችሁ ቅዱስ እንደ ሆነ እናንተ ደግሞ በኑሮአችሁ ሁሉ ቅዱሳን ሁኑ።" (1ኛ የጴጥሮስ መልእክት 1፥15-16)