Рет қаралды 165,050
Subscribe, Share like በማድረግ አገልግሎቱን ይደግፉ።
የተሸነፈ ትውልድ፤
አፍኒንና ፊንሃስ ሜዳ ላይ ቀርተዋል፤ ዔሊም አንገቱ ተሰብሮ መንገድ ዳር ሞቷል፡፡ ይህ ከሆነ በኋላ፤ ከአፍኒንና ከፊንሃስ ሚስት አንደኛዋ፤ በመጥፎው ዘመን መውለድ ስትጀምር፤ ተንበርክካ ወለደች፡፡ የልጁንም ስም፤ ‹‹ኢካቦድ›› አለችው፡፡ ኢካቦድ ማለት፤ የእግዚአብሔር ክብር ከእግዚአብሔር ሕዝብ ለቀቀ ማለት ነው፡፡ እዚህ ላይ፤ ውርደቱ በአካል ተረጋገጠ፡፡ ከዘርህ የሚቀር ቢኖር ዓይንህን ያፈዘዋል፤ ሰለተባለ፤ ያ የክፋትና የእርግማን ስም ከትውልድ ወደ ትውልድ እየተሸጋገረ መጥቶ፤ የእግዚአብሔር ክብር የለቀቀበት፤ የሐዘን፣ የሥቃይና የሽንፈት ትውልድ ላይ ደረሰ፡፡ ዛሬ በእኛ ኑሮ በዘመናችንና በመንፈሳዊ ጉዞአችን ውስጥ ያሉትን አንዳንድ ሁኔታዎች ስንመለከት፤ ከማሳደድ፣ ከመንቀል፣ ከወሬ፤ ከክፋት፤ ከምቀኝነት ወዘተ… ጋር የተያያዙ፤ በርካታ ከእግዚአብሔር ክብር የራቁ ምሳሌዎችን መጥቀስ እንችላለን፡፡ ምክንያቱም፤ ለአምልኮት ቦታና ጊዜ የለንም፡፡ ከዚህም በተጨማሪ፤ በዔሊ አምልኮት ማጣት ምክንያት የነበረው ተስፋ መቁረጥ፤ ዛሬም አብሮን አለ፡፡ ዔሊ አርባ ዓመት ሙሉ በውጣ ውረድ የኖረበት ሕይወት፤ ጠበኛና ሃፍረተ ቢስ ልጆችን ሲያስገኝለት እንኳን፤ ሊነቃ አልቻለም፡፡ ስለዚህ ቢወልድ፤ አፍኒን፣ ፊንሃስ፣ ኢካቦድ! አባቶች ያቆዩለትን በረከት፣ አደራና ክብር፤ መጠበቅ ያልቻለ ትውልድ ተፈጠረ፡፡ በአመዛኙ እኛም ልቦናችን ከአምላካችን ስለራቀ፤ ለእግዚአብሔር የተሰጡ ልጆች የሉንም፡፡ ለአዳል ሞቲ፣ ለወሰን ገፊ፣ ለጠቋር አባ ቡሌ፣ ለዛር አጋንንት፤ ወዘተ… ተስለን ሰለወለድን፤ የእኛና የልጆቻችን ዕድል፤ የመከራ ሆነ፡፡ የከፋ ችግር፣ ሐዘን፣ በሽታ፣ ስደት መታሰር፣ መገረፍ፣ መራብ፣ ወዘተ… የተለመዱና ቋሚ የኑሯችን መለያ ምልክቶች ሆኑ፡፡ በዛርና በውቃቢ መንፈስ የተለከፈ ማሕጸን፤ የሚያፈራው ደግሞ፤ ከእግዚአብሔር ክብር ራቀ ትውልድን፤ ኢካቦድን ነው፡፡ ‹‹ገለባን ትፀንሳላችሁ፤ እብቅንም ትወልዳላችሁ፤ እስትንፋችሁ የምትበላችሁ እሳት ናት፡፡›› ት/ኢሳ. 33÷11
የዔሊ፣ የአፍኒንና የፊንሐስ፤ የኢካቦድ ዘመን፤
አጠቃላይ መገለጫዎቹ፤
▪ ክብር የራቀውና የእግዚአብሔርን ታቦት ያስማረከ፤
▪ ታሪክ የወቀሰው አሳፋሪ ዘመን፤
▪ መሪና ተመሪ ያጣ (የተበተነ)፤ አባት የሌለውና ባዶውን የቀረ፤ መግቢያና መውጫው የጠፋው፣ ሰላም ያጣ ትውልድ፤
▪ ጠላት የሳቀበትና ያቃለለው፤ መተረቻና መዘባበቻ የሆነ፤
▪ የእርግማን ኃይል የገዛው፤
▪ ፍርሃት የተጠናተው የበረገገ ዘመን ነው፡፡
ቤተ-እግዚአብሔራችንን በቅድስና አለማገልገል፤
ቤተ-እግዚአብሔርን ከዓለም አንፃር ልዩ የሚያደርገው፤ የልብ፣ የአእምሮ፣ የሕሊናና የነፍስ የቅድስና ኃይል መኖሪያና መገለጫ በመሆኑ ነው፡፡እንዲሁም የእግዚአብሔር ተስፋና ራእይ ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዳይቋረጥ፤ ሰውና እግዚአብሔር የሚገናኙበት፤ ኃጢአትና የዲያብሎስ ሥራ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል የሚደመሰስበት፤ የአምላክ ምሕረትና ቸርነት የሚገለጥበት፣ በረከትና ሰላም፣ በፍቅርና ሞገስ፤ በእምነት የሰው ልጅ የሚያጎናጸፍበት ቅዱስ ሥፍራ፤የአምላክ ማደሪያ ቤተ-እግዚአብሔር ነው፡፡ከዚህ በተጨማሪ፤ የእግዚአብሔር ዳኝነት በመንፈሳዊውም፤ በሥጋዊውም መንገድ ላይ የሚታይበትና ሚዛናዊ ፍርድ ባለበት ሁኔታ፤ ቤተ-እግዚአብሔር፤ የጥበቃውና የኃይሉ ክንድም መግለጫ ነው፡፡ ቤተክርስቲያን የዚህ ሁሉ የመንፈሳዊ ኃይል ባለቤት ነች፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፤ በማቴ 16÷18 ላይ፤ ‹‹ የገሃነም ደጆችም አይችሉአትም›› ያላት ለዚህ ነው፡፡
የቤተ-እግዚአብሔር አንዳንድ አገልጋዮች ወጣ ያሉ ጠባዮች፤
▪ ቅድስናን የሚፈልጉ ቢሆንም፤ ውጊያው ግን ያስፈራቸዋል፤
▪ ቅድስና እንቢ ብሎት ተስፋ የቆረጠና፤ ሌላውን ተስፋ በሚያስቆርጥ ሁኔታ፤ የእግዚአብሔር መንግስት ከባድ ነው! እያሉ ሰውን የሚያስጨንቅና የወግ መዓት የሚያመጡና የሚያስፈራሩ ፤
▪ በቤተ እግዚአብሔር ሆኖ ዲያብሎስን የሚያገለግል፣ ምዕመናንን በመተት የሚያስር፣ የሐሜትና የተንኮል መንገድን የሚያስተምር፣ የአፍዝ አደንግዝ መኖሪያና የምትሐት አስተማሪ፣ የሐሰት መንፈስ መግለጫው ሆኖ የሚኖር፤
▪ በትርፍ አምልኮትና በጥቅም ላይ ብቻ አተኩሮ የሚኖር፣ የምዕመናን ለቅሶአቸው፣ ሐዘናቸውና ችግራቸው የማይሰማው፤ ለደሞዙና ለትርፍ ብቻ የሚኖር፤ በነጣቂ ተኩላ ተበሉ አልተበሉ፣ በአጋንንት መንፈስ ተያዙ፤ አልተያዙ ደንታ የሌለው፣ ዓላማና ግቡን የማያውቅ፣ የጥቅም ባለቤት፣ አምልኮት በሌለው አገልግሎቱ የሚመፃደቅ፣ የሚኮራና የሚታበይ፣ ለፍቅረ-ንዋይና ለሥልጣን ብቻ የሚያገለግል፤
▪ ጠላት ይቀድማል ብሎ የማያስብ ቸልተኛ አገልጋይ፣ የዲያብሎስን ሩጫ ያልተረዳ፣ የዛሬው የጥጋብ ጊዜ ለነገም ይሆናል! ብሎ የሚያምን፣ ለዕለት ደስታ ብቻ የሚኖር፣ ስለዲያብሎስ አሠራር ለማወቅም ሆነ ለመስማት የማይፈልግ፣ ዘመናዊነት ተጠናውቶት እያገለገለ፤ የሚያገለግለውን አምላክ የሚጠራጠር፣ መንፈሳዊነቱ የቀዘቀዘና በይበልጥ በዓለማዊነት ላይ የሚያተኩር፤
▪ መኖሪያው ቤተ እግዚአብሔር ሆኖ ሥራው መቶ በመቶ ዓለማዊ የሆነ፤ እሁድ ጧት ቤተ-እግዚአብሔር፣ ከሰዓት በኋላ ጠንቋይ ቤት፣ እሁድ ማታ ደግሞ፤ የምሽት ክበብ ውስጥ የሚገኝ፤ የዓለም ፍቅር የተጫነው፣ ከመንፈሳዊው መንገድ የራቀ ፍልስፍናን የሚሰብክ፣ የሥጋን ደስታ ሕይወቱ ያደረገ፣ የመቀደስን ቅድስና የማይወድ፣ የቤተ-እግዚአብሔር ጉብል ጥቂት አለመሆን፤
▪ ለሥልጣንና ለማዕረግ ዕድገት የሚሯሯጥ፣ የአቋራጭ የሥልጣን ከፍታን የሚያሳድድ፣ በሐሰት ወሬ በማቀበል ቅራኔ የሚዘራና ዕድገት እንደሚገኝ የሚያምን፣ በወንጀል ክስ የሚተዳደር፣ የወሬ ታማኝ ለመሆንና ጉቦ ለማቀበል እራሱን ለዚህ እርግማን ያዘጋጀ፣ ለቤተ እግዚአብሔርና ለምዕመናን የጽድቅ ቡራኬ መሆን ያቃተው፤
▪ ጽድቅንና የኢኮኖሚ ድጎማን ከመናፍቃን እየቀላወጡ፤ በቤተ እግዚአብሔር ሰዎች ሁለት ልብና ሁለት ኑሮ፣ ሁለት እምነት ያላቸው ለእምነት መጠናከር አርዓያ የሚያደርጉና ሃይማኖቱ የተሞታታባቸው፣ መነሻና መድረሻቸውን ያልለዩ፤ ድክመትን የሚፈላልጉና መናፍቅነትን የሚያራግቡ፤ ጥቂቶች አይደሉም፡፡
▪ ለአምልኮት ጸሎት ለሥራና ዕለት ለሚጠይቀው ፈጣን ክንውን ደንታ የሌለው፣ የጊዜው ፍጥነት የማይሰማው፣ በቢሮ አሠራር ቀጠሮን በማስረዘም ውሳኔን የሚጎትት፣ መማለጃ የለመደ ዓይኖቹና እጆቹ ያሉት፣ መንፈሳዊ ጥሪውንና የያዘውን እምነት፣ ኃላፊነት፣ ቦታና የእግዚአብሔርን ክብር የሚያሰድብ፣ ለቤተ እግዚአብሔር ታሪክና ለመንፈሳዊ አርዓያነት ቦታ የሌለው አገልጋይ ሁሉ፤ በተደጋጋሚ እንደተገለጸው፤ ራእይ አልባ የሆነው የልማዳዊው አገልግሎት ውጤት ነው፡፡ በመሆኑም፤ደንታቢስ አገልጋዮች በሚበዙበትና በበዙበት ዘመን፤ መንፈሳዊ ሕይወታችንን የሚያቀጭጨው፤ የክፋት አባት ዲያብሎስ ይደሰታል፡፡ በአጠቃላይ፤ እነዚህ ድክመቶች ባሉበት ወደ ሕዝብ ልንሄድ ቀርቶ፤ ራሳችንም ከዚህ ልማዳዊ አገልግሎት ወጥተን፤ ወደ ቅድስናው አምልኮት የምንደርስበት ኃይልና ጉልበት አጥተናል፡፡ ቤተክርስቲያን ከአምላካችን የተቀበለችው አደራ ግን፤
‹‹ኢየሱስም ቀረበና እንዲህ ብሎ ተናገራቸው፡- ሥልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጠኝ፡፡ እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኃቸው፣ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው፤ እነሆም እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ፡፡›› ማቴ 28÷18-20 የሚል ነው፡፡